
ኢ/ር ዘለቀ ረዲ ከወራት በፊት በተዋቀረውና አዲስ አመራሮችን በመረጠው አንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ውስጥ የውጭ ጉዳይ ኃላፊ ሆነው መመረጣቸው ይታወቃል፡፡ የሎሚ መፅሔት እውነትን ለህዝብ ለማድረስ ካለባት የሞያ ግዴታ አንፃር በኢ/ር ዘለቀ ዙሪያ በሚነሱ ሀሳቦች ላይ ተንተርሶ የሎሚ ም/አዘጋጅ ቶማስ አያሌው ያደረገውን ቆይታ የመጀመሪያ ክፍል እንደሚከተለው ቀርቧል፡፡
ሎሚ፡- አዲሱ የአንድነት ካቢኔ ሥራዎች እንዴት እየተከናወኑ ነው?
ኢ/ር ዘለቀ፡- በጣም ጥሩ ነው፡፡ ኢ/ር ግዛቸው በተለያዩ የአመራር ቦታዎች ላይ አዳዲስ ሰዎችን ነው ያመጣው፡፡ ከዛ አኳያ ጠንካራ ወይም ለቦታው ይመጥናሉ የተባሉ ሠዎች ናቸው የተመረጡት፡፡ ከዚህ ቀደምም ጠንካራ ሠዎች ነበሩ፡፡ አሁን ደግሞ የበለጠ ጠንካራ ሆነው ሊሠሩ የሚችሉ ሠዎች ናቸው የተመረጡት፡፡ እንደሚታወቀው አንድነት መሬት የረገጠ ፓርቲ ነው፡፡ ዝም ብሎ አየር ላይ የተንጠለጠለ ፓርቲ አይደለም፡፡ ከዛ አንፃር ሥራዎች በጥሩ ሁኔታ እየተከናወኑ ነው፡፡ አሁን ያለው አሠራር በዚሁ ከቀጠለ ጥሩ ውጤት ይመጣል የሚል እምነት አለኝ፡፡
ሎሚ፡- በርካቶች ግን አዲሱን የአንድነት ካቢኔ አወቃቀር አልወደዱትም ይባላል፤
ኢ/ር ዘለቀ፡- ከምን አንፃር?…ግልፅ አድርግልኝ?
ሎሚ፡- አንተን ጨምሮ ሌሎች ሁለት ሶስት ሰዎችን ማካተቱ ትክክል አይደለም የሚሉ ሂሶች ተሰንዝረዋል፡፡ ለምሳሌ፡- አንተን ከፓርቲው ለረጅም ጊዜ ርቆ ነበር፤ ራሱንም ማግለሉንም ተናግሮ ነበር፡፡ ቀደም ሲል በአመራርነት በነበረበት ጊዜ ድክመት ታይቶበት ነበር፡፡ እንደዚህ ዓይነት ችግሮች ያሉበት ሠው እንዴት በአመራር ደረጃ ሊመረጥ ይችላል የሚሉ ወገኖች አሉ፤
ኢ/ር ዘለቀ፡- አንዳንድ ነገሮችን ግልፅ ላድርግልህ፡፡ በመጀመሪያ ከፓርቲው ርቆ ነበር የሚለው ስህተት ነው፡፡ የፓርቲው አባል ነኝ፤ ከፓርቲውም ራሴን አላገለልኩም፤ ከስራ አስፈፃሚነት ራሴን አግልዬ ነበር፤ ከፓርቲው ግን አላገለልኩም፡፡ በብሔራዊ ም/ቤት ውስጥ እሰራ ነበር፡፡ በአባልነትም ቢሆን እሰራ ነበር፡፡ ሁልጊዜ ከፓርቲው ጋር እሰራ እንደነበር ነው የማስበው፡፡ ከፓርቲው ርቆ ፓርቲውን ለቆ ተመልሶ ወደ አንድነት መመለስ ትንሽ ከባድ ነው፡፡ አንድነት እንደ ሌሎች ፓርቲዎች አይደለም፡፡ አንድነት በጣም በነፃነት የሚሰራበት ፓርቲ ነው፡፡ እውነት ነው የምነግርህ፤ እኔ አንድነትን ለማስተዋወቅ አይደለም፡፡ ለምሳሌ ኢ/ር ግዛቸው ዛሬ ተነስቶ እኔ መስራት አይችልም ቢል ለምን የሚል ጥያቄ እንኳን አይቀርብበትም፡፡ እሺ ነው የሚባለው፡፡ ከአንድነት ሥራ አስፈፃሚው እለቃለሁ ሲል ለምን ትለቃለህ ብሎ የሚጠይቅ አልነበረም፡፡ መብትህ ነው፡፡ ማንም ሰው ከአባልነት እለቃለሁ ካለ የመልቀቅ ሙሉ መብት አለው፡፡ እመለሳለሁ ካለም ደግሞ ትቀበለዋለህ፡፡ ከፓርቲው ርቆ የነበረ ሰው ድጋሚ ልመለስ ቢል ትንሽ ከባድ ነው፡፡ አባላቱ ከባድ ናቸው፡፡ ብሔራዊ ም/ቤቱም እንደዚህ እንደምንገምተው አይደለም፡፡
ሎሚ፡- ከዚህ ቀደም ለሰንደቅ ጋዜጣ በሰጠኸው ቃለ ምልልስ ከስራ አስፈፃሚነት በራስህ ፍቃድ መልቀቅህን ተናግረህ ነበር፡፡ የፓርቲው ሊ/መንበር የነበሩት ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ ደግሞ አንተን ከቦታው ያነሱት እርሳቸው መሆናቸውን ይናገራሉ፡፡ ይሄን ነገር እንዴት ተመለከትከው?
ኢ/ር ዘለቀ፡- በዚህ ጉዳይ ምንም ባልል ደስ ይለኛል፡፡ ከዚህ ቀደም በእናንተ መፅሔት ላይ እርሳቸው ያሉትን አይቼዋለሁ፡፡ የመፅሔታችሁ ደንበኛ ነኝ፡፡ እርሳቸው እኔ ነኝ ያነሳሁት ብለዋል፡፡ ጥሩ፤ እርሳቸውም ያባሩኝ እኔም ልልቀቅ ችግር የለውም፡፡ አንድነት በነበሩበት ጊዜ ስለሰሩት በጎ ነገር አውርተዋል፡፡ ከበጎ ነገሮች አንዱ ደግሞ እኔን ማባረር ነው፡፡ ከዚህ ላይ ሊያገኙት የሚችሉት ትርፍ ምንድን ነው? እኔን የመሰለ ሠው፣ ራሱን ችሎ የሚንቀሳቀስ፣ የራሱ ሥራ ያለው፣ ፓርቲውን ሊደግፍ የሚችል ሰው ማባረራቸው ነው ውጤታማ ሥራቸው? በጣም በርካታ ሠዎችን አስገብተው እነገሌን አምጥቻቸዋለሁ ማለት ነው የሚሻለው ወይስ ኢ/ር ዘለቀን አባርሬዋለሁ?! እሺ እርሳቸው አባረሩኝ ብዬ ልውሰድ፤ ሰንደቅ ጋዜጣ በገዛ ፈቃዴ መልቀቄን ተከትሎ ጠይቋቸው ነበር፡፡ ያኔ “ኢ/ር ዘለቀ አለቀቀም፤ ሥራ እየሰራ እንደሆነ ነው የምናውቀው፡፡ አልሄደም አለቀቀም” ብለው ምላሽ ሰጥተዋል፡፡ በርሳቸው ዕድሜ ያለ ሰው ያንን ምስክርነት መካድ ይችላል?…ያኔ የተናገሩት ነገር መረጃ ነው፡፡ ወደኋላ ተመልሰው እኔን አባረውኝስ ቢሆን? መናገራቸው ምንድነው ትርፉ? እኔና እርሳቸው በዕድሜ በእጥፍ እንለያያለን፡፡ በዕድሜያቸው ብዙ ችሎታ አላቸው፤ ብዙ ለፍተዋል፡፡ ውጤት ማምጣት አለማምጣት የራሱ ጉዳይ ሆኖ ማለት ነው፡፡ እኚህ ሠው እኔ እንኳን በጣም መጥፎ ሠው ሆኜ ባስቸግር እንኳን መልሰው በጣም መጥፎ ሰው ነበር፤ እኔ ነኝ ያስተካከልኩት ቅርጽ ያስያዝኩት ቢሉ ነበር የሚሻለው፡፡ ኢ/ር ዘለቀን ያባረርኩት እኔ ነኝ ማለት ጀብደኝነትም አይደለም፡፡
አንድ ሰው ሊቀ-መንበር የሚሆነው ሰዎችን ለማባረር አይደለም፡፡ ደካማውን ማጠንከር ይጠበቅበታል፡፡ ማንም ሠው ደካማ ሊሆን ይችላል፡፡ እኔ በተፈጥሮዬ ደካማ አይደለሁም፡፡ ደካማ ብሆን ኖሮ አሁን ያለሁበት ቦታ ላይ አልገኝም ነበር፡፡ በትንሹ 150 ሠራተኞችን በስሬ አስተዳድራለሁ፡፡ ከ40 በላይ ቋሚ ሠራተኞች አሉኝ፡፡ ከ200 ሺህ ብር በላይ የወር ደመወዝ እከፍላለሁ፡፡ ይሔን ሁሉ የሚሰራ ሰው ደካማ ነው? ቤተሰቤንም ሆነ ሌሎች ሠዎችን ማስተዳደር የምችል ሠው ነኝ፡፡ ደካማ ብሆንም ከዶ/ር ነጋሶ የምጠብቀው “እንደዚህ ያለ ደካማ ነበር፤ እኔ ነኝ ጠንካራ ያደረግኩት” የሚል ምላሽ ነበር፡፡
ሎሚ፡- የአንድነት የዲሲፕሊን ኮሚቴ ሊቀጣህ የነበረበትና እንዲቀጣህ መመሪያ የተላለፈበት ሁኔታ ነበር?…
ኢ/ር ዘለቀ፡- ዶ/ር ነጋሶ ያላወቁት ነገር ሰው ወንጀለኛ ነው ጥፋተኛ ነው ተብሎ ሊከሰስ እንደሚችል ነው፡፡ አንድ ሌባ ፍርድ ቤት እስከሚፈርድበት ድረስ ተጠረርጣሪ እንጂ ወንጀለኛ አይባልም፡፡ ፍ/ቤቱ ትክክለኛ ውሳኔ እስከሚሰጠው ማለት ነው፡፡ የኔ ጉዳይም በዲሲፕሊን ያስቀጣል አያስቀጣም የሚለውን ማየት የነበረበት የዲሲፕሊን ኮሚቴ ነው አይደል? ያንን ዲሲፕሊን ኮሚቴ ደግሞ ማጠናከር የነበረባቸው ዶ/ር ናጋሶ ናቸው፡፡ እርሳቸው ያዳከሙትንና እርሳቸው የሌላቸውን ዲሲፕሊን ዲሲፕሊን ኮሚቴ ሊሰራው አይችልም፡፡ መጥተው ማቋቋም ይችላሉ፤ በሩ ክፍት ነው፡፡ እመጣለሁ ሲሉ አንድነት ይቀበላል፤ እሄዳለሁ ሲሉ ደህና ሁኑ ይላል፡፡ ጥፋት ኖሮብኝ ቢሆን ኖሮ እቀጣ ነበር፡፡ እርሳቸው ግን ውጭ ሆነው ይቆጫቸዋል፡፡ የኔ አለመቀጣት ትርፉን አላውቀውም፡፡ ፍ/ቤትም አለ እኮ፤ ከዛ ባለፈም እኔን መክሰስ ይቻላል፡፡ እኔ በእውነቱ የዲሲፕሊን ግድፈት አልነበረብኝም፡፡ ም/ቤቱ ዲሲፕሊን ኮሚቴ ይየው ብሏል አይደል? ይሄ ማለት ደግሞ ዘለቀ የዲሲፕሊን ግድፈት አለበት ማለት አይደለም፡፡ ዲሲፕሊን ኮሚቴውን አጠናክሮ እኔን ወደ ዲሲፕሊን ኮሚቴ ማቅረብ የነበረባቸው እርሳቸው ነበሩ፡፡ እውነት ለመናገር በእናንተ መፅሔት ላይ እንዳየሁት እኔ በፓርቲ መቀጠሌ ደስተኛ አላደረጋቸውም፡፡ እኔ ለቅቄ እወጣላቸዋለሁ፤ ችግር የለውም፡፡ ውጭ ሆኜ ፓርቲዬን መርዳት እችላለሁ፡፡ ዋናው ግን የሚያገኙት ትርፍ ምንድነው የሚለው ነው፡፡
ከመንግስት በኩል ብዙ ጫና አለብኝ፡፡ የኮንስትራክሽን ድርጅቴ ስምንት ዓመት ሆኖታል፡፡ እስካሁን ድረስ ግን ከመንግስት ሁለት ጊዜ ብቻ ነው የስራ ዕድል ያገኘሁት፡፡ ማንኛውም ኮንትራክተር የኮንደሚኒየም ሥራ የሚሰጠው ተጠርቶ ነው፡፡ የእኔ ድርጅት ግን ኮንዶሚኒየም ላይ አንድ ጠጠር አልጣለም፡፡ ለምን ቢባል ሊያዩኝ ስላልፈለጉ ነው፡፡ የኔ አንድነት ውስጥ መቀጠል ለምን ዶ/ር ነጋሶን ያበሳጫቸዋል? የሶስት ወር ጊዜ ነው የተሰጠን፡፡ አቅም ከሌለኝ የአንድነት ድርጅት አመንክም አላመንክም በሶተኛው ወር ዘለቀ አቅም የለውምና ይውጣ ይላል፡፡ ያንን ጊዜ መጠበቅ ያስፈልጋል፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ከኢህአዴግ ጎራ የወጡ ሰዎችን የዲሞክራሲው ትግል አጋር ማድረግ ነበረባቸው፡፡ እንጂ እኔም ላግዝ ብሎ የመጣውን የኔ ዓይነት ሰው አባረርኩት ማለት አይጠበቅባቸውም ነበር፡፡
ሎሚ፡- የአንድነት ፓርቲ የውጪ ግንኙነት ኃላፊ ነህ፡፡ ቦታው ትልቅ ነው፤ ይህንን ትልቅ ቦታ ያገኘኸው ደግሞ ፓርቲያችሁ አንድነት የሚሊዮኖች ድምፅ ለነፃነት የሚለውን እንቅስቃሴ ባዘጋጀበት ወቅት የገንዘብ ልገሳ ስላደረገ ለውለታው የተሰጠው ነው እንጂ ለቦታው የሚመጥን ሆኖ አይደለም ሲባል ነበር፤
ኢ/ር ዘለቀ፡- በርግጠኝነት ይሄን የሚሉ አዕምሮ ያላቸው ሠዎች ይኖራሉ ብዬ አልገምትም፡፡ ይሄ አንድነትን መናቅ ነው፡፡ አንድነት የት ቦታም እንዳለም አለማወቅ ነው፡፡ እውነቴን ነው የምነግርህ አንድነት ለብር ብሎ በህልውናው ላይ የሚደራደር ፓርቲ አይደለም፡፡ ይሄ የአዕምሮ ማነስም ጭምር ነው፡፡ ይሄ ማለት ዘለቀ አንድነትን በብር ይገዛዋል ብሎ ማሰብ ነው፡፡ አንድነትንም ማናናቅና መወንጀልም ጭምር ነው፡፡ የአንድነት ም/ቤት በሃገር፣ በህዝብ፣ በህልውና ላይ የማይደራደር ም/ቤት ነው፡፡ ዶ/ር ነጋሶ ሊቀ-መንበር በነበሩበት ጊዜ በአብላጫ ድምፅ የሚወሰነውን ነገር የመስራት ግዴታ አለባቸው አይደል? የራሳቸውን ልዩነት ግን በጋዜጣ ሁሉ ያራግቡ ነበር፡፡ ስለመድረክ ጉዳይ ልዩነት አለኝ ብለው ይፅፋሉ፡፡ ልዩነታቸውን እየፃፉ በአብላጫ ድምፅ ለመገዛት ደግሞ ህጉ ያስገድዳቸው ነበር፡፡ ስለዚህ ዘለቀ ለሚሊዮኖች ድምፅ ገንዘብ ስላወጣ ነው የተመረጠው ብሎ አንድነትን መናገር አሳፋሪ ነው፡፡
ሎሚ፡- ኢ/ር ዘለቀ የኢህአዴግ መልዕክተኛ ነው የሚሉ ወገኖች አሉ፤ ለዚህ አባባላቸው ደግሞ ካሉት ሶስት ም/ጠ/ሚኒስትሮች መካከል አንዱ የሆኑት አቶ ሙክታር ከድር የቅርብ ወዳጅና ከወዳጅነትም በላይ በአንድነት ውስጥ የማዳከምና የአንድነትን እቅስቃሴ ለመቅጨት ሰርጎ እንዲገባ የተደረገ መልዕክተኛ ነው ይባላል፡፡ አንተስ ሰምተሃል? ምንስ ትላለህ?